“ከአማራ ጋር ሂሳብ አወራርዳለሁ” የሚለው ትህነግ አገር መጋቢ በሆነው የአማራ ገበሬ ላይ ማሳ በማለስለሻውና በመዝሪያው ወቅት፣ በሐምሌ፣ ያወጀበት ጦርነት የአገር ደኅንነት ስጋት መሆኑን የጠቀሰው ዓለም አቀፍ የአማራ ማኅበራት ቃል፦
“አማራው በዜግነቱ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ በሚኖርባቸው የአገሪቱ ማዕዘናት በፖለቲካዊ እቅድ ተለይቶ ሲገደል፣ ሲፈናቀልና ሲሳደድ ለከፋ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተዳርጎ በችግር ሲማቅቅ በርካታ ዐሠርት አመታትን አሳልፏል። ይህ አንሶት ዛሬ “የለውጥ ዘመን” በሚባለው ጊዜ ከነዘር ምንዝሩ እየተጨፈጨፈ፣ የተገኘባቸው ቀዬዎችና ከተሞች እየወደሙ፣ በነፍስ የተረፈው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ህዝብ በአገሩ ስደተኛ ሆኖ አለበቂ መጠለያ የእለት ጉርስ ተመጽዋች ሆኖ ይገኛል”
ሲል የአማራውን ሁኔታ ይገልጻል።
የመርሀ ግብሩ አስተባባሪዎች ለማገር መገናኛ እንዳሳወቁት፣ ጦርነቱ በተከፈተባቸው ግንባሮች ሁሉ ህልውናውን ለማስከበርና አገሩን ለማዳን የሚዋደቀው ወገን የምግብና የመድኃኒት አቅርቦት ያስፈልገዋል። ዓለም አቀፍ የአማራ ማኅበራቱም
“ይህን በችግር ኖሮ አገር ደግፎ ያኖረ ህዝብ በዚህ ክፉ ቀን መደገፍ ኢትዮጵያን ማዳን ነው”
ሲሉ መላው አማራና አገሩን ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ገንዘብ በመለገስ ድጋፉን እንዲያሳይ ወገናዊ ጥሪ አቅርበዋል::